ሰሞኑን በትምህርት ሚኒስቴር ይፋ የተደረገው አቅጣጫ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን አመራሮች አመዳደብ ቀድሞ ከነበረው የብሔር ስብጥር አሰራር በመውጣት በችሎታ በቻ ተወዳድረረው የሚመደቡበት አሠራር ሊዘረጋ እንደሆነ ያሳያል።
ይህ ውሳኔ በአንደኛ እይታ እንደ ትልቅ “ሪፎርም” እና ተስፋ ሰጪ እርምጃ ሊታይ ይችላል። ይሁን እንጂ፣ የሀገሪቱን ነባራዊ የፖለቲካ ልምድ እና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን የተወሳሰበ ውድቀት መነሻ በማድረግ፣ ጉዳዩን ይበልጥ በጥልቀት ስንመረምረው፣ ከጀርባው ያሉትን ስር የሰደዱ ጥያቄዎች እና ስጋቶች መገንዘብ ያስፈልጋል።
የመንግስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላለፉት በርካታ አስርት ዓመታት የብሔር ፖለቲካ መፈልፈያ፣ የፓርቲ ካድሬዎች መደበቂያ እና የብቃት ማነስ ማሳያ ሆነው መቆየታቸው የአደባባይ ምስጢር ነው። አሁን ላይ “ከብሔር ስብጥር አሰራር ወጥተን በችሎታ ልንመድብ ነው” ተብሎ የሚነገረው ትረካ፣ ተቋማቱ አስከፊ የጥራት መውረድ አጋጥሟቸው፣ የዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተና (Exit Exam) ውጤት ተማሪዎች ሳይሆኑ ተቋማቱ ራሳቸው የወደቁ መሆናቸውን ካረጋገጠ በኋላ የመጣ የኋሊት ጩኸት ነው። ይህ መዘግየት በራሱ የፖለቲካው ውሳኔ የትምህርትን መዋቅር ምን ያህል እንዳደቀቀው ማሳያ ነው።
ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ዩኒቨርሲቲዎችን “ከማንኛውም የፖለቲካ ተፅዕኖ ነፃ ማድረግ” ስለሚለው አጀንዳ ደጋግመው ይናገራሉ። ይሁን እንጂ፣ በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ “ክፍት ውድድር” የሚባሉ የቅጥር ማስታወቂያዎች ራሳቸው በፖለቲካ ታማኝነት (Political Loyalty) እና በውስጥ መስመር ውሳኔዎች የሚጠለፉባቸው አጋጣሚዎች በርካታ ናቸው። ተቋማቱ በተግባር ነፃነታቸው ሳይረጋገጥ፣ በወረቀት ላይ በሚደረግ “ፈተና እና ውድድር” ብቻ አመራር ለመቀየር መሞከር፣ የድሮዎቹን ካድሬዎች በአዲሱ ገዥ መደብ ፍላጎት በሚስማሙ አዳዲስ “ቴክኖክራቶች” ከመተካት የዘለለ መዋቅራዊ ለውጥ ላያመጣ ይችላል። እውነተኛ ነፃነት የሚለካው አመራሩ በሚመረጥበት መንገድ ብቻ ሳይሆን፣ ተቋማቱ ከመንግስት ጣልቃ ገብነት ነፃ ሆነው በራሳቸው መተዳደር (Autonomy) ሲችሉ ብቻ ነው።
ዩኒቨርሲቲዎች በአሁኑ ወቅት የተጋረጡባቸው ችግሮች የአመራሮቹ የብሔር ስብጥር ብቻ አይደለም። ተቋማቱ በከፍተኛ የበጀት እጥረት፣ በደህንነት ስጋቶች፣ በካምፓስ ውስጥ አለመረጋጋት፣ እና በተመራማሪዎች የኑሮ መጓደል ሳቢያ ምሁራንን እያጡ ያሉ አቅመ-ቢስ መዋቅሮች ሆነዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ (ለምሳሌ በዓለም አቀፍ እና ቀጣናዊ ቀውሶች ሳቢያ በሚከሰት የኢኮኖሚ ጫና) የሚታየው የዋጋ ንረት እና የሪሶርስ እጥረት ባለበት ሁኔታ፣ የአመራር መምረጫ መስፈርቱን “በእውቀትና ችሎታ” ላይ ብቻ አደረግን ማለት ብቻውን ተቋማቱን የጥናትና ምርምር ማዕከል ሊያደርጋቸው አይችልም። መዋቅራዊ እና ፋይናንሺያል ድጋፍ ሳይኖር፣ ብቁ መሪዎችን ብቻ ወደ ወንበር ማምጣት በባዶ ሞተር ላይ ጎበዝ ሾፌር የማስቀመጥ ያህል ነው።