በሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ላይ ጠንካራ የተቃውሞ አቋም የያዙ የፖለቲካ እና የጦር መሪዎች፣ በትግራይ ክልል ላይ የፖለቲካና የወታደራዊ የበላይነትን መልሶ ለመያዝ ያለመ “የትግራይ ሰላምና ለውጥ ምክር ቤት” የተሰኘ አዲስ ተቋም በአዲስ አበባ መሥረታቸውን አስታወቁ።
በሕወሓት ከፍተኛ ጫና ምክንያት ከትግራይ ክልል ለመውጣት የተገደዱ የፖለቲካ ኃይሎች የተሳተፉበት ይህ ምክር ቤት፤ ክልሉን መልሶ ለመቆጣጠር በሚያስችሉ ስልቶች ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሠራ ተገልጿል።
እንደ አቶ ጌታቸው ረዳ እና ጀነራል ጻድቃን ገብረተንሳይ ያሉ ታዋቂ የሕወሓት ተቃዋሚዎች ግንባር ቀደም መሥራች የሆኑበት ይህ ምክር ቤት፣ ሰፊ ጥቅል ጥምረትን የፈጠረ መሆኑ ተነግሯል።
ከሲቪል ፖለቲከኞቹ ባሻገር፣ በአፋር ክልል ውስጥ እንደሚንቀሳቀስ የሚነገርለት የ“ሓራ መሬት” (የትግራይ ለውጥ ኃይል) ታጣቂ ቡድን ከፍተኛ አዛዥ ጀነራሎችም የዚህ ምክር ቤት አካል መሆናቸው ታውቋል።
የምክር ቤቱ መሥራቾች እና በአፋር ክልል የመሸገው የታጣቂ ቡድን አመራሮች ባለፉት ቀናት በአዲስ አበባ በነበራቸው ቆይታ፣ ህወሓትን ከሥልጣን አስወግዶ ትግራይን መልሶ ለመቆጣጠር በሚያስችል የጋራ ትግል ዙሪያ ሲመክሩ መሰንበታቸው ተገልጿል።
ምክር ቤቱ በትግራይ ክልል ውስጥ ያለውን ወቅታዊ የፖለቲካ አደረጃጀት በመቀየር፣ አዲስ የለውጥ ምዕራፍ ለመጀመር ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ ስልቶችን አቀናጅቶ እንደሚንቀሳቀስ ተጠቁሟል።
“የምክር ቤቱ መቋቋም በትግራይ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ አዲስ ኃይል መፈጠሩን የሚያሳይ ሲሆን፣ በቀጣናው ላይ ሊያስከትል የሚችለው የኃይል ሚዛን ለውጥ ከፍተኛ ትኩረትን ስቧል።”
እስከ አሁን ባለው መረጃ፣ በጉዳዩ ላይ ከሕወሓት በኩል የተሰጠ ይፋዊ ምላሽ የለም።